KOG,  የመጽሐፍ ቅዱስ ባህሪያት

ክፍል 8: እግዚአብሔር፤ ቃሉና ባሕሪው- ልዑል ንጉስ – ክፍል 2

(የእግዚአብሔር ልኡላዊነትና የመንግስቱ መገለጥ)


በብሉይ ምንም እንኳ የእግዚአብሔር መንግሥት ባይብራራም ነገር ግን የእግዚአብሔር አገዛዝ በፍጥረት፤ በሰማይና በምድር ባሉ ተቀሳቃሽ ፍጡራን፤ በዚህ ዓለም ላይ ባሉ መንግሥታትና ነገስታት ላይ እንደዚሁም ደግሞ በተለየ መልኩ በራሱ ፍጹም ነጻ የጸጋ አነሳሽነት ጠርቶና ዋጅቶ ገንዘቡ ባደረገው ሕዝቡ ላይ መንገሱ በይፋ ግልጽ ሆኖ የሚታይ ክስተት ነበር። ይህም የአንዱ የእግዚአብሔር ሉዓላዊ መንግሥት ነው!


የእግዚአብሔር ሉዓላዊነት (ጌትነንትና ገዢነት) በሁለት መልኩ ተገልጧል። ሉዓላዊ ጌትነት እግዚአብሔር ራሱን ለፍጥረቱ የሚገልጥበት መንገድ ነው። እግዚአብሔር በፍጥረቱ ላይ በመፍጠር፤ በመመገብ፤ በመቤዠት ሆነ በመፍረድ እንደሚሰራ ተመልክተናል። እነዚህንም ሥራዎች ሲሰራ ለፍጥረቱ ጌትነቱን ለመግለጽ ነው።

  • ማሳሰቢያ፡ ጌትነት የእግዚአብሔር የውስጥ ሕይወት ወደውጪ መንጸባረቁን ያመለክታል እንጂ በክበበ-ሥላሴ የውስጥ እርስበርስ ሕይወት የጌታና የሎሌ ግንኙነት የለውም። ይህ ግንኙነት “ሁሉን የፈጠረው የሥሉሱ እግዚአብሔር” እና “የፍጥረቱ ግንኙነት ነው።”
  • ይህም ጌትነት/ልዕልና በሁለት መልኩ ይገለጻል።
    1. የሁሉ ጌታ፡ ወሰን-መጠቅ/ሉዓላዊ ጌትነት (Universal/Providential Kingdom) ሲሆን፡ ይህ መንግስት ሰማይንና ምድርን ያካለለ ነው፤ አገዛዙም ፍጥረቱን ሁሉ የሚሞላ ልዕልና ነው። በመንፈሱም በፍጥረቱ ወዲህና ወዲያ እየተንቀሳቀሰ ያስተዳድራል!
    2. የሕዝቡ ጌታ፡ ታዳጊ/ ኪዳናዊ ጌትነት (Particular/Redemptive Kingdom) ሲሆን ግዛቱ ገንዘቡ የሆነ ሕዝቡ ሲሆን፤ በሕላዌነቱ በመካከላቸው በመረጠው ሥፍራ አብሯአቸው ይኖራል! በኤደን ለመጀመሪያውቹ ሰዎች ለአዳምና ለሔዋን፤ በመገናኛው ድንኳን ለእሥራኤል በምድረበዳ ፤ በጽዮን በቤተ-መቅደሱ ሥፍራ፤ በኢየሱስ ሰውነት ከመስቀል በፊት፤ ከተነሳ በኋላ ደግሞ በምድር በቤተክርስቲያን፤ በሰማይ “በአዲሲቱ ኢየስሩሳሌም/ ጽዮን ተራራ” በመጨረሻ ከሰማይ ወደምድር በምትወርደው አዲሲቱ ሰማይና አዲስቱ ምድር እግዚአብሔር እጅ ባልሰራው መቅደስ ከሕዝቡ ጋር ለዘላለም ይኖራል!
  • ሁለቱም የሚገልጹት የአንዱ የእግዚአብሔርን መንግሥት ሁለት ገጽታዎች ናቸው። እግዚአብሔር ለፈጠርው ፍጥረት ጌትነቱን ሲገልጽ ልዕልናውን በነዚህ በሁለት መልኮች ይገልጣል ማለታችን ነው።

እ/ር በትድግና ጌትነቱን ለሕዝቡ ሲገልጥ አላማው ጌትነቱን ለምድርና ለሰማይ ለመግለጥ ነው። ስለዚህ አጥብበን ያየነው የእግዚአብሔር አገዛዝ አላማው ጌትነቱን ለምድር ሁሉ ለመግለጥ ነው።

 

በመጀመሪያ የእግዚአብሔር መንግስት ሥንል ታድያ ምን ማለታችን ነው?

  • የእግዚአብሔር መንግሥት፡ ስንል ምን ማለታችን ነው?
    1. አገዛዝ፡ ስለ እግዚአብሔር መንግስት መጽሀፍ ቅዱስ ሲናገር በመጀመሪያ ደረጃ የሚናገረው ስለ “አስተዳደር” ወይም አገዛዝ Sovereign rule ሲሆን።
    2. የግዛት ክልል፡ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ አገዛዙ የሚገለጥበትን ክልል (Realm)ለማመልከት ነው።
  • ሥልጣን ማለት የመግዛት መብት ማለት ነው (ምሳ፡ ሉቃ 19፡ 11-12)
  •  ሰማይና ምድር፡ ይህ አገላለጽ በተለያዩ አገባቦች የተለያዩ ትርጉሞች አሉት፡ ለምሳሌ
    • ሰማይ በመጽሀፍ ቅዱስ የእግዚአብሔርን ፍጹም ሥልጣን መመንጫ ሆኖ ወክሎ ሲገባ፤ ምድር ደግሞ ሥልጣኑ የሚገለጥበትን ክልል ይወክላል።

      ኢሳ 66፡ 1-2እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ሰማይ ዙፋኔ ነው፥ ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት፤ የምትሠሩልኝ ቤት ምን ዓይነት ነው? የማርፍበትስ ስፍራ ምንድር ነው? 2 እነዚህን ሁሉ እጄ ሠርታለችና እነዚህ ሁሉ የእኔ ናቸው ይላል እግዚአብሔር፤

    • ሰማይና ምድር፡ ጠቅላላ እግዚአብሔር የፈጠረውን ፍጥረት ይገልጻል

      ዘፍ 1:1 “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ”

    • በአዲስ ኪዳን ሰማይ ኢየሱስ የማዳን ሥራውን ፈጽሞ ወደአባቱ የሁሉ ጌታ ይሆን ዘንድ ሲያርግ በግርማው ቀኝ የተቀመጠበት ሥፍራ ነው። እስኪመለስ ድረስ በዚያ ሆኖ ይቆያል። በዚህ ሥፍራ አሁን ቤተክርስቲያንን ራስ ሆኖ የሚያስተዳድርበት የሽግግር መንግሥት ነው። (ሐዋ 3፡ 21፤)

      Ephesians 1:20–23 ክርስቶስንም ከሙታን ሲያስነሣው ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይና በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ሊመጣ ባለው ዓለም ደግሞ ከሚጠራው ስም ሁሉ በላይ በሰማያዊ ስፍራ በቀኙ ሲያስቀምጠው በክርስቶስ ባደረገው ሥራ የብርታቱ ጉልበት ይታያል፤ 22 ሁሉንም ከእግሩ በታች አስገዛለት ከሁሉ በላይም ራስ እንዲሆን ለቤተ ክርስቲያን ሰጠው። 23 እርስዋም አካሉና ሁሉን በሁሉ የሚሞላ የእርሱ ሙላቱ ናት።

እነዚህን ሁለት ልዩነቶች አጉልተው የሚያሳዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ሐቲት እንመልከት፡

የእግዚአብሔርን አገዛዝ

  • መዝ 145:11–13
    “ሥለ መንግሥትህ ክብር ይናገራሉ፥
    “ሥለ ኃይልህንም ይነጋገራሉ፥
  • በዚህም ብርቱ ሥራህን፤
    የመንግሥትህን ግርማ ክብር ያስታውቃሉ
    መንግሥትህ የዘላለም መንግሥት ናት፥
    ግዛትህም ለልጅ ልጅ ነው።”
  • ዳንኤል 4:3–4
     ተአምራቱ እንዴት ታላቅ ነው!
    ድንቁም እንዴት ጽኑ ነው!
    መንግሥቱም የዘላለም መንግሥት ነው፥
    ግዛቱም ለልጅ ልጅ ነው።
በዕብራይስጥ የግጥም አገጣጠም መርህ መሰረት፤ የመጀመሪያው የግጥም አንጓ የሁለተኛውን አንጓ ሐሳብ ወይ ይቃረናል ወይንም ይመሳሰላል። ለምሳሌ በአማርኛ የመጀመሪያው አንጓ “በክብር” ካለቀ ሁሉእተኛው አንጓ የግድ በ “ር” የሚጨርስ ቃል መሆን አለበት። የእብራይስጡ ግን ከአራቱ የግጥም መርህ አንዱ ተመሳሳይ ቃሎችን ማስገባት ነው። ለምሳሌ “ብርሃን” በሚል ቃል የዕብራይስጡ ግጥም ወይ በጨለማ ወይም በወገግታ ቃል ይገጥማል ። ምክኒያቱም አንዱ ይቃረናል ሌላኛው ይመሳሰላል። ልክ አንደዚሁ “መንግሥት” ለሚለው ቃል ዘማሪው ተመሳሳይ ቃል ሲጠቀም ኃይልና ግዛት የሚሉትን ቃሎች በመጠቀም የእግዚአብሔር መንግሥት ስንል ምን ማለታችን እንደሆን ይተረጉምልናል። መንግሥት ማለት የእግዚአብሔር ኃይል ማለት ነው። መንግሥት ማለት የእግዚአብሔር አገዛዝ/ ግዛት ማለት ነው። 
  • ሉቃ 17:20 “ፈሪሳውያንም። የእግዚአብሔር መንግሥት መቼ ትመጣለች ብለው ቢጠይቁት፥ መልሶ። የእግዚአብሔር መንግሥት በመጠባበቅ አትመጣም፤ 21 ደግሞም። እንኋት በዚህ ወይም። እንኋት በዚያ አይሉአትም። እነሆ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት በመካከላችሁ ናትና አላቸው።”
  • ቆላ 1:13–14 እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።

የእግዚአብሔርን የግዛት ክልል፡ 

  • ማቴ 8:11–13 “እላችኋለሁም፥ ብዙዎች ከምሥራቅና ከምዕራብ ይመጣሉ ከአብርሃምና ከይስሐቅ ከያዕቆብም ጋር በመንግሥተ ሰማያት ይቀመጣሉ፤ 12 የመንግሥት ልጆች ግን በውጭ ወደ አለው ጨለማ ይጣላሉ፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል። 13 ኢየሱስም ለመቶ አለቃ። ሂድና እንዳመንህ ይሁንልህ አለው። ብላቴናውም በዚያች ሰዓት ተፈወሰ።”
  • ማቴ 13:41–42 “የሰው ልጅ መላእክቱን ይልካል፥ ከመንግሥቱም እንቅፋትን ሁሉ ዓመፃንም የሚያደርጉትን ይለቅማሉ፥ 42 ወደ እቶነ እሳትም ተጣሉ
  • ማቴ 26:26–29 “ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ባረከ ቈርሶም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጠና። እንካችሁ፥ ብሉ ይህ ሥጋዬ ነው አለ። 27 ጽዋንም አንሥቶ አመስግኖም ሰጣቸው እንዲህም አለ። ሁላችሁ ከእርሱ ጠጡ፤ 28 ስለ ብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው። 29 ነገር ግን እላችኋለሁ፥ በአባቴ መንግሥት ከእናንተ ጋር ከዚህ ከወይን ፍሬ አዲሱን እስከምጠጣበት እስከዚያ ቀን ድረስ ከዛሬ ጀምሬ አልጠጣውም።”
  • ራዕ 5:9–10

    መጽሐፉን ትወስድ ዘንድ ማኅተሞቹንም ትፈታ ዘንድ ይገባሃል፥ ታርደሃልና፥ በደምህም ለእግዚአብሔር ከነገድ ሁሉ ከቋንቋም ሁሉ ከወገንም ሁሉ ከሕዝብም ሁሉ ሰዎችን ዋጅተህ ለአምላካችን መንግሥትና ካህናት ይሆኑ ዘንድ አደረግሃቸው፥ በምድርም ላይ ይነግሣሉ እያሉ አዲስን ቅኔ ይዘምራሉ።
  • ራዕ 11:15–17
    “ሰባተኛው መልአክ ነፋ፤ በሰማይም። የዓለም መንግሥት ለጌታችንና ለእርሱ ለክርስቶስ ሆነች፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣል 16 የሚሉ ታላላቅ ድምፆች ሆኑ። በእግዚአብሔርም ፊት በዙፋኖቻቸው የተቀመጡ ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በግምባራቸው ተደፍተው 17 ለእግዚአብሔር እየሰገዱ እንዲህ አሉ። ያለህና የነበርህ ሁሉን የምትገዛ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፥ ትልቁን ኃይልህን ስለ ያዝህ ስለ ነገሥህም እናመሰግንሃለን፤”
  • ራዕ 21:1–8
    አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም። 2 ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ። 3 ታላቅም ድምፅ ከሰማይ። እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ 4 እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና ብሎ ሲናገር ሰማሁ። 5 በዙፋንም የተቀመጠው። እነሆ፥ ሁሉን አዲስ አደርጋለሁ አለ። ለእኔም። እነዚህ ቃሎች የታመኑና እውነተኛዎች ናቸውና ጻፍ አለኝ። 6 አለኝም። ተፈጽሞአል። አልፋና ዖሜጋ፥ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ። ለተጠማ ከሕይወት ውኃ ምንጭ እንዲያው እኔ እሰጣለሁ። 7 ድል የሚነሣ ይህን ይወርሳል አምላክም እሆነዋለሁ እርሱም ልጅ ይሆነኛል። 8 ዳሩ ግን የሚፈሩና የማያምኑ የርኵሳንም የነፍሰ ገዳዮችም የሴሰኛዎችም የአስማተኛዎችም ጣዖትንም የሚያመልኩ የሐሰተኛዎችም ሁሉ ዕድላቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፤ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው።

ወሰን-መጠቅ ጌትነት (Universal Kingdom) እና የኪዳን ጌትነት

የእግዚአብሔር ገዢነቱ፤ ንግሥናውና ሥልጣኑ መንግስቱ የተመሰረተው በፈጣሪነቱ ነው። እነዚህም ፍጥረታት ለክብሩ-መገለጫ ይሆኑ ዘንድ በነጻ ፈቅዶ የፈጠራቸው የእጆቹ ሥራዎች ናቸው።

ምሳሌ፡ አራቱ እንሥሣት ፍጥረትን ወክለው (ወሰን-መጠቅ ጌትነት) እንደዚሁም ደግሞ 24ቱ ሽማግሌዎች የተዋጁትን የእግዚአብሔርን ሕዝብ ወክለው (የኪዳን ጌትነት) ሲያመሰግኑ ይታያሉ። ራዕ 4:10-11)

በነዚህ ሁለቱ ዓይነት አገዛዙ የተጎናጸፋቸው ስሞቹ፡ “ኤል፤ ኤሎሂም“-የሁሉ ጌትነቱን ሲያንጸባርቅ፤ “ያህ-ያህዌ” የተባለው የግል-የህላዌ ስሙ ደግሞ ኪዳናዊ/ ታዳጊ አገዛዙን ይገልጣል!

  • ምጡቅ-ፈጣሪነቱ፡ ይህም ዓለምት በቃሉ እንደ ተዘጋጁ፥ ሁሉንም ነገር ካለመኖር ወደመኖር ያመጣና የሚታየው ነገር ሁሉ በማይታየው በእርሱ መፈጠራቸው ነው። ይህንን ክብር በላቲን “creatio ex nihilo (“creation out of nothing”፤ ከባዶ ውስጥ የወጣ ፍጥረት)”
    • Genesis 1:31 “እግዚአብሔርም ያደረገውን ሁሉ አየ፥ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ። ማታም ሆነ ጥዋትም ሆነ፥ ስድስተኛ ቀን።”
  • ምጡቅ ሕያውነቱ፦ በራሱ ሕያው የሆነና ምሉዕ የሆነው አምላክ ለፍጥረቱ ሁሉ እስትንፋስ መሰረት መሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር የፍጥረቱ ገዢ እንዲሆን እንዳደረገው ይናገራል፡
    • ኤር10፡10 እግዚአብሔር ግን እውነተኛ አምላክ ነው፤ እርሱም ሕያው አምላክና የዘላለም ንጉሥ ነው፤”
    • Deuteronomy 5:26 “ከሥጋ ለባሽ ሁሉ እኛ እንደ ሰማን በእሳት ውስጥ ሆኖ ሲናገር የሕያው አምላክን ድምፅ ሰምቶ በሕይወቱ የኖረ ማን ነው?
    • መዝ 42፡2 ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፤ መቼ እደርሳለሁ? የአምላክንስ ፊት መቼ አያለሁ?
  • ለአግዚአብሔር የጌትነት መሰረት ፈጣሪነቱና ሕያውነቱ ስለመሆኑ የተሰጠ ሐቲት
    • Genesis 14:19 የልዑል እግዚአብሔር ካህን የነበረው የሳሌም ንጉሥ መልከ ጼዴቅም…እንዲህ ሲል ባረከው፤ ሰማይንና ምድርን የፈጠረ ልዑል አምላክ (ኤል-ኤልዮን) አብራምን ይባርክ፤ ጠላቶችህን አሳልፎ በእጅህ የሰጠህ ልዑል አምላክ (ኤል-ኤልዮን)
      ይባረክ።
    • Genesis 14:22–24 አብራምም የሰዶምን ንጉሥ አለው። ሰማይንና ምድርን ወደሚገዛ ወደ ልዑል አምላክ (ኤል-ኤልዮን) እጄን ከፍ አድርጌአለሁ፤ አንተ አብራምን ባለጠጋ አደረግሁት እንዳትል፥ ብላቴኖቹ ከበሉት በቀር ከእኔ ጋር ከሄዱትም ድርሻ በቀር፥ ፈትልም ቢሆን የጫማ ማዘቢያም ቢሆን፥ ለአንተ ከሆነው ሁሉ እንዳልወስድ፤ አውናን ኤስኮልም መምሬም እነርሱ ድርሻቸውን ይውሰዱ።
    • Exodus 20:8–11 የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ። 9 ስድስት ቀን ሥራ ተግባርህንም ሁሉ አድርግ፤ 10 ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር ለአምላክህ ሰንበት ነው፤ ….11 እግዚአብሔር በስድስት ቀን ሰማይንና ምድርን፥ ባሕርንም፥ ያለባቸውንም ሁሉ ፈጥሮ በሰባተኛው ቀን ዐርፎአልና፤ ስለዚህ እግዚአብሔር የሰንበትን ቀን ባርኮታል ቀድሶታልም።
      • የእግዚአብሔር እረፍት በፈጠረው ሁሉ ላይ መንገሱን ያሳያል
        Genesis 1:31 2:1–3 “እግዚአብሔርም ያደረገውን ሁሉ አየ፥ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ። ማታም ሆነ ጥዋትም ሆነ፥ ስድስተኛ ቀን። “ሰማይና ምድር ሠራዊታቸውም ሁሉ ተፈጸሙ። 2 እግዚአብሔርም የሠራውን ሥራ በሰባተኛው ቀን ፈጸመ፤ በሰባተኛውም ቀን ከሠራው ሥራ ሁሉ ዐረፈ። 3 እግዚአብሔርም ሰባተኛውን ቀን ባረከው ቀደሰውም፤ እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፎአልና።”
      • የመገንኛው ድንኳን ሥራ በፍጥረት ሥራ ተመስሏል፡ “Exodus 39:42–43 “እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘ ሁሉ እንዲሁ የእስራኤል ልጆች ሥራውን ሁሉ ሠሩ። 43 ሙሴም ሥራውን ሁሉ አየ፥ እነሆም አድርገውት ነበር፤ እግዚአብሔር እንዳዘዘው እንዲሁ አድርገውት ነበር፤ ሙሴም ባረካቸው።
      • እግዚአብሔር ከመገንኛው ድንኳን ሆኖ ሕዝቡን ይመራል፡ Exodus 40:33–38 (AMHB) በማደሪያውና በመሠዊያውም ዙሪያ አደባባዩን ተከለ፤ የአደባባዩንም ደጃፍ መጋረጃ ዘረጋ። እንዲሁም ሙሴ ሥራውን ፈጸመ። 34 ደመናውም የመገናኛውን ድንኳን ከደነ፥ የእግዚአብሔርም ክብር ማደሪያውን ሞላ። 35 ደመናውም በላዩ ስለ ነበረ የእግዚአብሔርም ክብር ማደሪያውን ስለ ሞላ ሙሴ ወደ መገናኛው ድንኳን ይገባ ዘንድ አልቻለም። 36 ደመናውም ከማደሪያው በተነሣ ጊዜ የእስራኤል ልጆች በመንገዳቸው ሁሉ ይጓዙ ነበር። 37 ደመናው ባይነሣ እስከሚነሣበት ቀን ድረስ አይጓዙም ነበር። 38 በመንገዳቸውም ሁሉ በእስራኤል ቤት ሁሉ ፊት የእግዚአብሔር ደመና በማደሪያው ላይ በቀን ነበረና፥ እሳትም በሌሊት በዚያ ላይ ነበረና።
      • ሰለሞን ቤተመቅደሱን በሰባት ዓመት ሰርቶ ጨረሰ (1ነገ 6:38)፤ የተመረቀው በሰባተኛው ወርና ለሰባት ቀን በሚከበር በዳስ በዓል ነው (እግዚአብሔር ከስራው በሰባት ቀን እንዳረፈ እንደዚሁም በሕዝቡ መካከል የመንግሥቱ መገለጫ የሆነው የቤተ-መቅደሱም ሥራ በሥነ ፍጥረት ሥራ መመሰሉን ሲያሳይ በሰባት ዓመት ሥራው ተጠናቀቀ )፡
        • 1 Kings 8:10–43 “ካህናቱም ከመቅደሱ በመጡ ጊዜ ደመናው የእግዚአብሔርን ቤት ሞላው። 11 የእግዚአብሔርም ክብር የእግዚአብሔርን ቤት ሞልቶ ነበርና ካህናቱ ከደመናው የተነሣ ለማገልገል ይቆሙ ዘንድ አልቻሉም። 12 ሰሎሞንም። እግዚአብሔር። በጨለማው ውስጥ እኖራለሁ ብሎአል፤ 13 እኔም ለዘላለም የምትኖርበት ማደሪያ ቤት በእውነት ሠራሁልህ አለ። በውኑ እግዚአብሔር ከሰው ጋር በምድር ላይ ይኖራልን? [ምጡቅነቱ] እነሆ፥ ሰማይ ከሰማያትም በላይ ያለው ሰማይ ይይዝህ ዘንድ አይችልም፤ ይልቁንስ እኔ የሠራሁት ቤት እንዴት ያንስ! ነገር ግን፥ አቤቱ አምላኬ ሆይ፥ ወደ ባሪያህ ጸሎትና ልመና ተመልከት፥ ዛሬም ባሪያህ በፊትህ የሚጸልየውን ጸሎትና ጥሪውን ስማ፤…41–43 ከሕዝብህም ከእስራኤል ወገን ያልሆነ እንግዳ ታላቁን ስምህን፥ ብርቱይቱንም እጅህን፥ የተዘረጋውንም ክንድህን ሰምቶ ስለ ስምህ ከሩቅ አገር በመጣ ጊዜ፥ መጥቶም ወደዚህ ቤት በጸለየ ጊዜ፥ 43 አንተ በማደሪያህ በሰማይ ስማ፤ የምድርም አሕዛብ ሁሉ ስምህን ያውቁ ዘንድ እንደ ሕዝብህም እንደ እስራኤል ይፈሩህ ዘንድ፥ በዚህም በሠራሁት ቤት ስምህ እንደተጠራ ያውቁ ዘንድ፥ እንግዳው የሚለምንህን ሁሉ አድርግ።
      • እግዚአብሔር በሰባተኛው ቀን እንድረፈ በመቅደሱ ሥፍራ በጽዮን አርፏል፡ “Psalm 132:7–8 ወደ ማደሪያው እንግባ፤ እግሮቹ በሚቆሙበት ስፍራ እንስገድ 8 እግዚአብሔር ሆይ ተነሥ አንተና የሐይልህ ታቦት ወደ ማረፊያ ሥፍራ ሂዱ…13እግዚአብሔር ጽዮንን መርጧታልና፤ ማደሪያውም ትሆን ዘንድ ወዷልና እንዲህ አለ፡ ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ናት፤ ፈልጌያታለሁና በእርሷ እኖራለሁ!”
      • እግዚአብሔር ሕዝቡን ከባርነት ቤት አውጥቶ እየመራ የወሰዳቸው ወደ ክብሩ ማደሪያሥፍራ ነበር። ሕዝቡን ገንዘቡ ያደርግ ዘንድ የገለጠው ክብርና ህያው ስም (ያህዌ) መንግስቱን ገለጠ Exodus 15: 11–14 “አቤቱ፥ በአማልክት መካከል እንደ አንተ ያለ ማን ነው? በምስጋና የተፈራህ፥ ድንቅንም የምታደርግ፥ በቅድስና የከበረ እንደ አንተ ያለ ማን ነው? 12 ቀኝህን ዘረጋህ፥ ምድርም ዋጠቻቸው። 13 በቸርነትህ የተቤዠሃቸውን ሕዝብህን መራህ፤ (ኪዳናዊ ጌትነት) በኃይልህ ወደ ቅዱስ ማደሪያህ አገባሃቸው። 14 አሕዛብ ሰሙ፥ ተንቀጠቀጡም፤ በፍልስጥኤም የሚኖሩትን ምጥ ያዛቸው። 15 የዚያን ጊዜ የኤዶም አለቆች ደነገጡ፤ የሞአብን ኃያላን መንቀጥቀጥ ያዛቸው፤ በከነዓን የሚኖሩ ሁሉ ቀለጡ። 16 አቤቱ፥ ሕዝብህ እስኪያልፍ ድረስ፥ የተቤዠኸው ሕዝብ እስኪያልፍ ድረስ፥ ፍርሃትና ድንጋጤ ወደቀባቸው፤ በክንድህ ብርታት እንደ ድንጋይ ዝም አሉ። 17 አቤቱ፥ አንተ ታስገባቸዋለህ፥ በርስትህ ተራራም ትተክላቸዋለህ፥ አቤቱ፥ ማደሪያህ ባደረግኸው ስፍራ፥ አቤቱ፥ እጆችህ ባዘጋጁት መቅደስ። 18 እግዚአብሔር ለዘላለሙ እስከ ፍጻሜ ይነግሣል።
      • Jeremiah 10:1–7 (AMHB)
        • 1 እናንተ የእስራኤል ቤት ሆይ፥ እግዚአብሔር በእናንተ ላይ የተናገረውን ቃል ስሙ። 2 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። የአሕዛብን መንገድ አትማሩ ከሰማይ ምልክትም አትፍሩ፤ አሕዛብ ይፈሩታልና። 3 የአሕዛብ ልማድ ከንቱ ነውና፤ ዛፍ ከዱር ይቈረጣል፥ በሠራተኛም እንጅ በመጥረቢያ ይሠራል። 4 በብርና በወርቅ ያስጌጡታል፥ እንዳይናወጥም በችንካርና በመዶሻ ይቸነክሩታል። 5 እንደ ተቀረጸ ዓምድ ናቸው እነርሱም አይናገሩም፤ መራመድም አይቻላቸውማን ይሸከሙአቸዋል። ክፉ መሥራትም አይቻላቸውምና፥ ደግምም መልካም ይሠሩ ዘንድ አይችሉምና አትፍሩአቸው። 6 አቤቱ፥ እንደ አንተ ያለ የለም፤ አንተ ታላቅ ነህ ስምህም በኃይል ታላቅ ነው። 7 የአሕዛብ ንጉሥ ሆይ፥ በአሕዛብ ጥበበኞች ሁሉ መካከል በመንግሥታቸውም ሁሉ እንደ አንተ ያለ ስለሌለ፥ አንተን መፍራት ይገባልና አንተን የማይፈራ ማን ነው?

          …10 እግዚአብሔር ግን እውነተኛ አምላክ ነው፤ እርሱም ሕያው አምላክና የዘላለም ንጉሥ ነው፤ ከቍጣው የተነሣ ምድር ትንቀጠቀጣለች፤ አሕዛብም መዓቱን አይችሉም። 11 እናንተም። ሰማይንና ምድርን ያልፈጠሩ እነዚህ አማልክት ከምድር ላይ ከሰማይም በታች ይጠፋሉ ትሉአቸዋላችሁ። 12 ምድርን በኃይሉ የፈጠረ፥ ዓለሙን በጥበቡ የመሠረተ ሰማያትንም በማስተዋሉ የዘረጋ እርሱ ነው። 13 ድምፁን ባሰማ ጊዜ ውኆች በሰማይ ይሰበሰባሉ፥ ከምድርም ዳር ደመናትን ከፍ ያደርጋል፤ ለዝናቡም መብረቅን ያደርጋል፥ ነፋስንም ከቤተ መዛግብቱ ያወጣል። 14 ሰው ሁሉ እውቀት አጥቶ ሰንፎአል፥ አንጥረኛም ሁሉ ከቀረጸው ምስል የተነሣ አፍሮአል፤ ቀልጦ የተሠራ ምስሉ ውሸት ነውና፥ እስትንፋስም የላቸውምና። 15 እነርሱ ምናምንቴና የቀልድ ሥራ ናቸው፤ በተጐበኙ ጊዜ ይጠፋሉ። 16 የያዕቆብ እድል ፈንታ እንደ እነዚህ አይደለም፤ እርሱ የሁሉ ፈጣሪ ነውና፤ እስራኤልም የርስቱ ነገድ ነውና፤ ስሙ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ነው።

      • ሥለዚህ የእግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጥሮ ማረፉ የመንግሥቱ ክብር መንሰራፋቱን ያመለክታል
    • 2 Kings 19:14-15 “ሕዝቅያስም (የአሦር ንጉስ የጻፈውን ደብዳቤውን ከመልእክተኞች እጅ ተቀብሎ አነበበው፤ ሕዝቅያስም ወደ እግዚአብሔር ቤት ወጥቶ በእግዚአብሔር ፊት ዘረጋው። ሕዝቅያስም ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ጸለየ። በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ የእስራኤል አምላክ አቤቱ፥ አንተ ብቻህን የምድር ነገሥታት ሁሉ አምላክ ነህ፤ ሰማይንና ምድርን ፈጥረሃልና።16 አቤቱ፥ ጆሮህን አዘንብልና ስማ፤ አቤቱ፥ ዓይንህን ክፈትና እይ፤ በሕያው አምላክ ላይ ይገዳደር ዘንድየላከውን የሰናክሬምን ቃል ስማ። 17 አቤቱ፥ በእውነት የአሦር ነገሥታት አሕዛብንና ምድራቸውን አፍርሰዋል፥ 18 አማልክቶቻቸውንም በእሳት ላይ ጥለዋል፤ የእንጨትና የድንጋይ የሰው እጅ ሥራ ነበሩ እንጂ አማልክት አልነበሩምና፤ ስለዚህ አጥፍተዋቸዋል። 19 እንግዲህም አምላካችን አቤቱ፥ የምድር መንግሥታት ሁሉ አንተ ብቻ እግዚአብሔር አምላክ እንደ ሆንህ ያውቁ ዘንድ ከእጁ እንድታድነን እለምንሃለሁ። 20 የአሞጽም ልጅ ኢሳይያስ እንዲህ ብሎ ወደ ሕዝቅያስ ላካ። የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ስለ አሦር ንጉሥ ስለ ሰናክሬም ወደ እኔ የለመንኽውን ሰምቻለሁ። 21 እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የተናገረው ቃል ይህ ነው። ድንግሊቱ የጽዮን ልጅ ቀላል አድርጋሃለች፥ በንቀትም ስቃብሃለች፤ የኢየሩሳሌም ልጅ በላይህ ራስዋን ነቅንቃብሃለች። 22 የተገዳደርኸው፥ የሰደብኸውስ ማን ነው? ቃልህንስ ከፍ ከፍ ያደረግኸው ዓይንህንም ወደ ላይ ያነሣኸው በማን ላይ ነው? በእስራኤል ቅዱስ ላይ ነው። 23 አንተስ። በሰረገላዬ ብዛት ወደ ተራሮች ከፍታ፥ ወደ ሊባኖስ ጥግ ላይ ወጥቻለሁ፤ ረጃጅሞቹንም ዝግባዎች የተመረጡትንም ጥዶች እቈርጣለሁ፥ ወደ አገሩም ዳርቻና ወደ ቀርሜሎስ ዱር እገባለሁ። 24 ቈፈርሁም፥ እንግዳውንም ውኃ ጠጣሁ፤ የተገደበውንም ውኃ ሁሉ በእግሬ ጫማ አደርቃለሁ ብለህ በመልእክተኞችህ እጅ በእግዚአብሔር ላይ ተገዳደርህ። 25 እኔ ጥንቱን እንደ ሠራሁት፥ ቀድሞውንም እንዳደረግሁት አልሰማህምን? አሁንም የተመሸጉትን ከተሞች የፍርስራሽ ክምር እስኪሆኑ ድረስ እንድታፈርስ አደረግሁህ። 26 ስለዚህም የሚኖሩባቸው ሰዎች እጃቸው ዝሎአል፥ ደንግጠውም ታውከዋል፤ እንደ ምድረ በዳ ሣር፥ እንደ ለምለምም ቡቃያ፥ በሰገነትም ላይ እንዳለ ሣር፥ ሳይሸት ዋግ እንደ መታውም እህል ሆነዋል። 27 እኔ ግን መቀመጫህንና መውጫህንም መግቢያህንም፥ በእኔም ላይ የተቈጠኸውን ቍጣ አውቄአለሁ። 28 ቍጣህና ትዕቢትህ ወደ ጆሮዬ ደርሶአልና ስለዚህ ስናጋዬን በአፍንጫህ፥ ልጓሜንም በከንፈርህ አደርጋለሁ፥ በመጣህበትም መንገድ እመልስሃለሁ።
    • Psalm 96:4–10 (AMHB) 4 እግዚአብሔር ታላቅ ምስጋናውም ብዙ ነውና፥ በአማልክትም ሁሉ ላይ የተፈራ ነውና። 5 የአሕዛብ አማልክት ሁሉ አጋንንት ናቸውና፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ። 67 የአሕዛብ ወገኖች፥ ለእግዚአብሔር አምጡ፥ ክብርና ምስጋናን ለእግዚአብሔር አምጡ፤ 8 ለስሙ የሚገባ ክብርን ለእግዚአብሔር አምጡ፤ ቍርባን ያዙ ወደ አደባባዮችም ግቡ። 9 በቅድስናው ስፍራ ለእግዚአብሔር ስገዱ፤ ምድር ሁሉ በፊቱ ትነዋወጥ። 10
      በአሕዛብ መካከል። እግዚአብሔር ነገሠ በሉ። እንዳይናወጥም ዓለሙን እርሱ አጸናው፥ አሕዛብንም በቅንነት ይፈርዳል።
    • Isaiah 42:5–8 “ሰማያትን የፈጠረ የዘረጋቸውም፥ ምድርንና በውስጥዋ ያለውን ያጸና፥ በእርስዋ ላይ ለሚኖሩ ሕዝብ እስትንፋስን፥ ለሚሄዱባትም መንፈስን የሚሰጥ አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እኔ እግዚአብሔር በጽድቅ ጠርቼሃለሁ፥ እጅህንም እይዛለሁ እጠብቅህማለሁ፥ የዕውሩንም ዓይን ትከፍት ዘንድ የተጋዘውንም ከግዞት ቤት በጨለማም የተቀመጡትን ከወህኒ ቤት ታወጣ ዘንድ ለሕዝብ ቃል ኪዳን ለአሕዛብም ብርሃን አድርጌ እሰጥሃለሁ። 8 እኔ እግዚአብሔር ነኝ፤ ስሜ ይህ ነው፤ ክብሬን ለሌላ፥ ምስጋናዬንም ለተቀረጹ ምስሎች አልሰጥም።
    • Is 40:12–28
    • Isaiah 43:15–19 ቅዱሳችሁ፥ የእስራኤል ፈጣሪ፥ ንጉሣችሁ፥ እግዚአብሔር እኔ ነኝ። 16 እግዚአብሔር በባሕር ውስጥ መንገድን በኃይለኛም ውኃ ውስጥ መተላለፊያን ያደርጋል፤ 17 እግዚአብሔር ሰረገላውንና ፈረሱን ሠራዊቱንና አርበኛውን ያወጣል፤ እነርሱ ግን በአንድነት ተኝተዋል፥ አይነሡም፤ ቀርተዋል፥ እንደ ጥዋፍ ኩስታሪም ጠፍተዋል፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። 18 የፊተኛውን ነገር አታስተውሉ፥ የጥንቱንም ነገር አታስቡ። 19 እነሆ፥ አዲስ ነገርን አደርጋለህ፤ እርሱም አሁን ይበቅላል፥ እናንተም አታውቁትምን? በምድረ በዳም መንገድን በበረሀም ወንዞችን አደርጋለሁ።
    • Isaiah 44:24

      ከማኅፀን የሠራህ፥ የሚቤዥህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል ። ሁሉን የፈጠርሁ፥ ሰማያትን ለብቻዬ የዘረጋሁ ምድርንም ያጸናሁ እግዚአብሔር እኔ ነኝ፤ ከእኔ ጋር ማን ነበረ?

    • Isaiah 45:5–8

      እኔ እግዚአብሔር ነኝ ከእኔም ሌላ ማንም የለም፤ ከእኔም በቀር አምላክ የለም፤ በፀሐይ መውጫና በምዕራብ ያሉ ከእኔ በቀር ማንም ሌላ እንደሌለ ያውቁ ዘንድ አስታጠቅሁህ፥ አንተ ግን አላወቅኸኝም…7 ብርሃንን ሠራሁ፥ ጨለማውንም ፈጠርሁ፤ ደኅንነትን እሠራለሁ፥ ክፋትንም እፈጥራለሁ፤ እነነዚህን ሁሉ ያደረግሁ እግዚአብሔር እኔ ነኝ። 8 እናንተ ሰማያት ከላይ አንጠባጥቡ ደመናትም ጽድቅን ያዝንቡ፤ ምድርም ትከፈት መድኃኒትንም ታብቅል፥ ጽድቅም በአንድነት ይብቀል፤ እኔ እግዚአብሔር ፈጥሬዋለሁ። 9 ከሠሪው ጋር ለሚታገል ወዮለት! በምድር ሸክላዎች መካከል ያለ ሸክላ ነው። ጭቃ ሠሪውን። ምን ትሠራለህ? ወይስ ሥራህ። እጅ የለውም ይላልን? 10 አባትን። ምን ወልደሃል? ወይም ሴትን። ምን አማጥሽ? ለሚል ወዮ….21 ይናገሩ ይቅረቡም በአንድነትም ይማከሩ፤ ከጥንቱ ይህን ያሳየ ከቀድሞስ የተናገረ ማን ነው? ያሳየሁም የተናገርሁም እኔ እግዚአብሔር አይደለሁምን? ከእኔም በቀር ሌላ አምላክ የለም፤ እኔ ጻድቅ አምላክና መድኃኒት ነኝ፥ ከእኔም በቀር ማንም የለም። 22 እናንተ የምድር ዳርቻ ሁሉ፥ እኔ አምላክ ነኝና፥ ከእኔም በቀር ሌላ የለምና ወደ እኔ ዘወር በሉ ትድኑማላችሁ። 23 ቃሌ ከአፌ በጽድቅ ወጥታለች፥ አትመለስም። ጕልበት ሁሉ ለእኔ ይንበረከካል፥ ምላስም ሁሉ በእኔ ይምላል ብዬ በራሴ ምያለሁ።

እግዚአብሔር የሁሉ ፈጣሪ ሥለሆነ አለሙን ሁሉ ይገዛል ደግሞም ሕዝቡን ይገዛል

  • Psalm 103:19–22 (AMHB)
    19 እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አዘጋጀ፥ መንግሥቱም ሁሉን ትገዛለች። 20 ቃሉን የምትፈጽሙ፥ ብርቱዎችና ኃያላን፥ የቃሉንም ድምፅ የምትሰሙ መላእክቱ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ። 21 ሠራዊቱ ሁሉ፥ ፈቃዱን የምታደርጉ አገልጋዮቹ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ። 22 ፍጥረቶቹ ሁሉ በግዛቱ ስፍራ ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ባርኩ። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ።
  • Psalm 145:13

    መንግሥትህ የዘላለም መንግሥት ናት፥ ግዛትህም ለልጅ ልጅ ነው።

  • Psalm 47:2

    እግዚአብሔር ልዑል ግሩምም ነውና፥ በምድር ሁሉ ላይም ታላቅ ንጉሥ ነውና።

  • Daniel 2:37
    አንተ፥ ንጉሥ ሆይ፥ የሰማይ አምላክ መንግሥትንና ኃይልን፥ ብርታትንና ክብርን የሰጠህ የነገሥታት ንጉሥ አንተ ነህ።

    Daniel 5:21

    ልዑል አምላክም በሰዎች መንግሥት ላይ እንዲሠለጥን፥ የሚወድደውንም እንዲሾምበት እስኪያውቅ ድረስ ከሰው ልጆች ተይለቶ ተሰደደ፥ ልቡም እንደ አውሬ ልብ ሆነ፥ መኖሪያውም ከምድረ በዳ አህዮች ጋር ነበረ፤ እንደ በሬ ሣር በላ፥ አካሉም በሰማይ ጠል ረሰረሰ።

  • Numbers 23:21–23

    “በያዕቆብ ላይ ክፋትን አልተመለከተም፥ በእስራኤልም ጠማምነትን አላየም፤ አምላኩ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነው፥ የንጉሥም እልልታ በመካከላቸው አለ። 22 እግዚአብሔር ከግብፅ አውጥቶአቸዋል፤ጕልበቱ አንድ ቀንድ እንዳለው ነው። 23 በያዕቆብ ላይ አስማት የለም፥ በእስራኤልም ላይ ምዋርት የለም፤ በጊዜው ስለ ያዕቆብና ስለ እስራኤል። እግዚአብሔር ምን አደረገ! ይባላል።”

የመንግሥቱ ሁለቱ ገጽታዎች በአስተርእዮ እድገት

እግዚአብሔር ፍጥረትን ሲፈጥር ፍጹም ፍጥረት ባይሆንም ነገር ግን ሁሉም መልካም እንደሆን አየ። ከላይ እንደተመለከትነውም በሰባተኛው ቀን አረፈ!

የእግዚአብሔር መንግሥትና ፍጥረት

  • ሰውንም እንደ አምሳሉ በመፍጠር በፈጠርው ነገር ላይ ሾመው፡ የንግሥና ሹመት

    Genesis 1:26–28

    26 እግዚአብሔርም አለ። ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ።

    27 እግዚአብሔርም ሰውን በመልኩ ፈጠረ፤

    በእግዚአብሔር መልክ ፈጠረው፤

    ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው።

    28 እግዚአብሔርም ባረካቸው፥ እንዲህም አላቸው። ብዙ፥ ተባዙ፥ ምድርንም ሙሉአት፥ ግዙአትም፤ የባሕርን ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው።

  • ነገር ግን ይህን ሹመትና ሃላፊነት የሚወጣው የእግዚአብሔርን ወሰን-መጠቅ ሥልጣኑን በምትገልጠው በኤደን ገነት መካከል ባለችው ዛፍ ተምሳሌትነት ለተሰጠው ትዕዛዝ ሲገዛ ብቻ ነው። ይህም የክህነት ሥራው ነበር።
    • ኤደን የሥልጣን ሥፍራ ናት ዛፉም የእግዚአብሔርን የሥልጣን ትእዛዝ/ መንግሥት ትወክላለች። ይህ ፍጥረት ጌታ አለው፤ ጊታውም ሰው አይደለም።
      • 8 እግዚአብሔር አምላክም በምሥራቅ በዔድን ገነትን ተከለየፈጠረውንም ሰው ከዚያው አኖረው።….16 እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው። ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ 17 ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና።
    • ኤደን የእግዚአብሔር ሕላዌ የሚገለጥባት የመቅደስ ምሳሌ ናት
      • Genesis 3:8 እነርሱም ቀኑ በመሸ ጊዜ የእግዚአብሔርን የአምላክን ድምፅ ከገነት ውስጥ ሲመላለስ ሰሙ
    • የአዳም በኤደን ገነት የተሰጠው ሥራ የንግሥና ሥራ ሳይሆን የክህነት ሥራ ነበር፤
      • Genesis 2:15 (AMHB) አራተኛውም ወንዝ ኤፍራጥስ ነው። እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ወስዶ ያበጃትም ይጠብቃትም ዘንድ በዔድን ገነት አኖረው።

የእግዚአብሔር መንግሥትና የሰው ውድቀት


One Comment

  • kassahuntm

    ውድ ወንድሞችና እህቶች፤

    በጌታ ፍቅር ሰላም እላችኋለሁ።

    አለማወቅን ( ignorance) በጣም ፈራለሁ፤ ሳይታወቅ ወደ ጥፋት ሊያመራ ይችላልና። ባለሁበት ደረጃ በተለይ ከእግዚአብሄር ቃል ጋር በተያያዘ መልኩ ሳየዉ አለማወቅ በጣም አስጊ ነገር ነዉ። ምክንያቱም የእግዚአብሄር ቃል ከህይወት ጋር የተያያዘ ነዉና! ታድያ ትክክለኛዉን ካላወቅሁ ሥህተትን እንዳልከተል እንዴት ልጠበቅ እችላልሁ? ትክክለኛዉን ገንዘብ ወይም ብር በዉል የማያውቅ ሰዉ የተጭበረበረውን ይዞ ወደ ቤቱ የማይሄድበት ምን ምክንያት አለ? በነገራችን ላይ በሃሰት ገንዘብ የአገር ኢኮኖሚ እንዳይወድቅ ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረገው በመስኩ ብቃት ያላቸዉ ኤክስፐርቶችን በማስልጠንና በማሰማራት ነዉ። የስልጠናዉን አብይ ድርሻ የሚይዘዉና ስልጠናዉም የሚጀምረው ትክክለኛዉን ገንዘብ በጥልቀት በማጥናት ነዉ። እንዲያዉም ለማስረጃ ያህል ካልሆነ በቀር የተጭበረበሩ ገንዘቦችን በማጥናት ጊዜ አያባክኑም፤ ትክክለኛዉ ገንዘብ ከታወቀ የሃሰት የሆነዉን መለየት ጊዜ አይወስድምና። እንዲሁም የክርስቲያን ትምህርት/ የትምህርተ መለኮት መሰረተ ሃሳብ የጨበጠ ሰዉ በስህተት ትምህርት አይታለልም። በኣጭሩ ከስህተት ትምህርት የምንድነው መጽሐፍ ቅዱስን በሚገባ ተምረን በማወቅ ነው፤ በዚህ Summer እየተማርን ያለነዉም ወደዚሁ ግብ የሚያመራን ነዉ።

    ወንድሞችና እህቶች፤

    አሁን በክፍልና ( On line) ላይ ሳሚ እያስተማረን ያለዉ እጅግ በጣም አስፈላጊና መሰረታዊ እንድሆነ ተረድቻለሁ። ይህን ትምህርት ከጀመርኩ ወዲህ መጽሐፍ ቅዱስ ሳነብ ያለኝ መረዳት በጅጉ ተለዉጧል። በጣምም ደስ አለኝና ሁላችሁንም አሰብኩ! በኑሮአችን የምናደርጋቸዉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ እናዉቃለን። ነገር ግን በተቻለ መጠን ጨክነን በክፍል የሚሰጠዉን እንከታተል፤ ያልቻልን ደግሞ samsontblog.getayesus.com በመጎብኘት እናንብብ፣ እናድምጥ። ያም ብቻ አይደለም፣ እግዚአብሄር ሌሎችንም ወደዚህ አገልግሎት እንዲመራና ተጠቃሚ እንዲሆኑ እንጸልይ። እንዲሁም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ በአግልግሎታቸዉ የባረኩን ወገኖችና ቤተሰኦቻቸዉን በጸሎት እናስብ። እግዚአብሄር በእነርሱ እንደባረከን ሁሉ እኛም በረክት እንድንሆናቸው ያብቃን።

    ጌታ በነገሮች ሁሉ ከእናንተ ጋር ይሁን፣

    ካሣሁን ነኝ

Leave a Reply to kassahuntm Cancel reply

Your email address will not be published.